myEthiopia.com
  • ደወል

​አሁንስ ዳኛው ማነው?

10/11/2020

0 Comments

 
ዋካንዳ ዘኢትዮጵያ
 
ዳኛው ማነው? የተሰኘውን በአምባሳደር ታደለች ኃ/ሚካኤል የተጻፈውን መጽሐፍ አንብቤ ስጨርስ እርሳቸው የጠየቁትን ጥያቄ ለመመለስ ሳወጣና ሳወርድ በመጽሐፋቸው ውስጥ ብዙ“ዳኞችን”አየሁ:: ጉልበት፣ ጠብመንጃ፣ ባለጊዜ፣ አድርባይነት፣ ርዕዮተ ዓለም በአንድ ወገን ሆነው ያሻቸውን ፍርድ ሲሰጡ፥ እንደ ኩራዝ ብርሃን ጭል ጭል የምትል በጎ ሕሊና ደግሞ ግራ ቀኙን በመመልከት እፁብ ድንቅ የሚያስብል ዳኝነትን ስትሰጥ ትታያለች:: አምባሳደር ታደለችም ይህችን በጎ ሕሊና ሲያዩ “እንዴት ሊሆን ቻለ?”በማለት አግራሞትና ጥያቄ እንደፈጠረባቸው ተገንዝቤያለሁ::እኔ እንደገባኝ የእርሳቸው የ“ዳኛው ማነው?” ጥያቄ በመግቢያው ላይ የፍትሕ በመውጫው ላይ ደግሞ የታሪክ ዳኝነትን ነው:: 
 
ዳኛ፦ ግራ ቀኙን መመልከት እንዲችል መኻል ላይ ያለ ሰው ወይም ተቋም ነው:: በአገራችን የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ ግን መኻል መሆን ተወዳጅ አይደለም:: በደርግ ዘመን “መኻል ሰፋሪዎች ሚናችሁን ለዩ” በማለት መኻል ላይ የቆመ ዳኛ እንዳይኖር ተደርጓል:: መኻል ላይ የነበሩ ልክ “ከወንድሞቿ በላይ ከፍ እንዳለች ማሽላ ወይ ለወፍ አለበለዚያ ለወንጭፍ” እንደሚባለው ለአንዱ ሲሳይ ሆነዋል:: በኢህአዴግ ዘመንም ቢሆን መኻል የሚባል የለም:: አንድ ሰው በቅንነት ለአገርና ለወገን ይጠቅማል ብሎ የሚናገረውን አሳብ የነ እገሌ አሳብ ነው በማለት ይፈረጃል::  ስለዚህ የአንድ ጎልማሳ ሰውን እድሜ ያክል፥ በአገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ ጭል ጭል ከምትለዋ በጎ ኅሊና በስተቀርተቋሟዊ የሆነ እውነተኛ ዳኛ አለ ለማለት ያስቸግራል:: ይህ ልምምድ ለኅምሳ ዓመታት እንደ ሸረሪት ድር አእምሯችንን ተብትቦ ስለያዘው፥ዳኝነትን የምናየው ከራሳችን አቋም አንጻር ብቻ ነው:: ስለዚህ በዳይና ተበዳይን በትክክል ለመለየት አልተቻለም:: ባለጊዜ የወደቀውን ጥፋተኛ ያደርጋል፤ እርሱ ሲወድቅ ደግሞ በሌላ ባለጊዜ ጥፋተኛ ይባላል፤ ያ በመጀመሪያ ጥፋተኛ የተባለው ደግሞ ከወደቀበት አንሰራርቶ እኔ ጥፋተኛ አልነበርኩም ይላል:: እንዲህ እንዲህ እያለ እስከዛሬ ደርሰናል:: በታሪክም ሆነ በትርክት መግባባትና መስማማት አዳጋች ሆኗል:: መወገን እንጂ መኻል ላይ ቆሞ እንደ ባለ አእምሮ ማሰብ እንደ ክፉ ነገር ተወስዷል::
 
ከእውነተኛ ዳኝነት ይልቅ “ሕጋዊንና ሕገወጥነትን” ቀላቅሎ መሄድ እንደ ትክክለኛ የትግል አቅጣጫ ይታያል:: ከዚህም የተነሳ ዳኝነትን የሚያዛቡ ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ድርጊቶችን በእለት ተእለት ሕይወታችን ማየት እንግዳ አይደለም::ከእኛ በተቃራኒ የቆሙት ላይ ሕጋዊ ርምጃ ሲወሰድ መንግሥትን ማወደስ፥ በእኛ ላይ ሲሆን ግን መንግሥትን መሳደብ ወይም የሽምግልና ጋጋታማብዛት  ልማድ ሆኗል:: ለራስ የፓለቲካ ግብ ጥቅም ይሁን እንጂ ሕገ መንግሥትን ማክበርም ይሁን መጣስ ምንም ልዩነት የላቸውም:: ሕዝብን ለማደናገር ሕገ መንግሥት ሲጣስም ሳይጣስም ተጣሰ ብሎ መጮህ ለጆሮ የሰለቸ “ሙዚቃ” ነው::ሰዎች በግፍ ከቀያቸው ሲፈናቀሉ ዝም ያለ “አክቲቪስት” አፈናቃዮች በቁጥጥር ስር ሲውሉ ሰብአዊ መብት ተጣሰ ይላል:: መኻል ላይ የቆሙ ሰዎችና ተቋሟት በሌሉባት አገር “ባለጊዜ” እንጂ “ዳኛ” ሊኖር አይችልም::
 
ከሁለት ዓመት በፊት የተጀመረው ለውጥ ሲመጣ “ተደምረሃል?” የሚለው ጥያቄ በተራው ሰው ዘንድ በስፋት ይጠየቅ የነበረው መኻል ላይ መሆን ትክክል አይደለም ከሚለው አጉል አባዜ የመነጨ ነው:: ለለውጡ ድጋፉን ለመግለጽ አዲስ አበባን ያጥለቀለቀው የሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም ሰልፍ ተሳታፊ፥ በአገር ውስጥከሚኖሩትም ሆነ ከውጭ ከመጡ ግለሰቦችና ድርጅቶች “ኪስ” ውስጥ ለመግባት ብዙም ጊዜ አልወሰደበትም:: ምክንያቱም የለመድነው ጎራ ለይቶ መጎሻሸም እንጂ መኻል ላይ ቆሞ ግራ ቀኙን መመልከት አይደለም:: ወደ ግራም ሆነ ወደ ቀኝ ፈጥኖ ከመግባት መኻል ላይ ቆሞና መዝኖ የሚበጀውን መምረጥ የተሻለ ነበር:: 
 
እንግዲህ እውነተኛ ዳኛ የምንፈልግ ከሆነ መኻል ላይ የቆሙ ግለሰቦችና ተቋሟት ያስፈልጉናል:: ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሲቪክ ማኅበራት ተወካዮች ጋር በነበራቸውየውይይት  ጊዜ “ሲቪክ ሶሳይቲ ሚዛን የሚያስጠብቅ” ነው በማለት መኻል ላይ ያለ ተቋምን አስፈላጊነት ተናግረዋል:: ይህ መኻልላይ ላሉና ለመሆን ለሚፈልጉ ትልቅ ተስፋ ነው:: ምክንያቱም ከረጅም ዓመታት በኋላ መኻልላይ መቆም ጥሩ መሆኑን ከገዢው ፓርቲና መንግሥት በይፋ ስለሰማን ነው:: ይህ መልካም ጅምር ከግብ እንዲደርስ የፓለቲካ ፓርቲዎችና መንግሥት መኻል ላይ ያሉ ተቋማትን ለራስ ፍላጎት መጠቀሚያ ከማድረግ መቆጠብ ይኖርባቸዋል:: ተቋማቱም የመንግሥትና የፓለቲካ ፓርቲዎች መጠቀሚያ ከመሆን ራስን ማጽዳት ይጠበቅባቸዋል:: ይህ ሲሆን በአገራችን ኢትዮጵያ ዳኛ ይኖራል፣ ዴሞክራሲም ያብባል፣ በጎ ሕሊና ያላቸው ትልቅ ሰዎችም ይበዛሉ::
 
ከዚህ በተጨማሪ ብዙ የተባለለት የፍትሕና ርትእ አካሉ መኻል መሆን እጅግ አስፈላጊ ነው:: በዚህ አካል ላይ የፓርቲዎችም ሆነ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት ለቡድን እንጂ ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም፣ መልካም አስተዳደር፣ እድገትና ዴሞክራሲ ጥቅም የለውም:: በጎ ሕሊና ያላቸው፣ መኻል ላይ የቆሙ፣ ለእውነት ተገዢ የሆኑ፣  ለገንዘብ የማይጓጉ፣ እግዚአብሔርን የሚፈሩ፣ ሰውን የሚያከብሩ፣ በሙያቸውና በስብእናቸው የተከበሩ ሰዎችን በዚህ ተቋም ውስጥ ማብዛት እውነተኛ ዳኛ እንዲኖረን ያደርጋል:: 
 
የኃይማኖት ተቋማትም መኻል ነበሩ ማለት አይቻልም:: ባለጊዜና ጉልበተኛ ወደፈለገው ሲጎትታቸው፣ እንደፈለገው ሲያምሳቸው ብዙ ዓመታትን አስቆጥረዋል:: ዛሬም ቢሆን ሳይጎተቱ ለመጎተት ራሳቸውን ያዘጋጁ፣ ጭርስኑ ጎራ ለይተው ከፓለቲከኞች የማያንስ የመከፋፈል ሥራ የሚሠሩ የኃይማኖት መሪዎች ይስተዋላሉ:: በግላቸው የፈለጉትን መሆን ይችላሉ፤ ተቋሙን ግን መኻል ላይ እንዲቆም መተው ለኃይማኖቱም ለአገርም ይጠቅማል:: ምክንያቱም የኃይማኖት ተቋማት መኻል መሆን በጎ ሕሊናና ሚዛናዊነት ያላቸው ዜጎችን በማዘጋጀት እውነተኛ ዳኞች እንዲኖሩን ያደርጋል:: በእኔ እይታ እስካሁን ድረስ በሙስሊሙም ሆነ በክርስቲያኑ ዘንድ የዳኝነትን ማዕረግ የተጎናጸፉ ተቀዳሚ ሙፍቲ ሃጂ ዑመር እድሪስ ይመስሉኛል::እርሳቸውን ያነሳሁት ታዋቂ ስለሆኑ ነው እንጂ ብዙ ሰው የማያውቃቸው፣ ሚዛናዊ የሆኑ፣ የሚመሩትን ምዕመን በጎ ሕሊና እንዲኖረውና እንዲያመዛዝን የሚያስተምሩ መኖራቸውን አውቃለሁ:: እንደ እነዚህ ዓይነት ያሉ መሪዎችን በሁሉም የእምነት ተቋማት ፈጣሪ እንዲያበዛልን ምኞቴ ነው::
 
ሰው አእምሮ ያለው ፍጡር ነው:: የተፈጠረውም ማመዛዘን እንዲችል ሆኖ ነው:: ስለዚህ የሰው ልጅ የሆነ ሁሉ መኻል ላይ በመቆም የሠራቸውንና የሄደበትን ጎዳና ለማየት ከሕሊናው ጋር የሚሟገትበት ጊዜ ሊኖረው ይገባል:: በራሱ ላይ ዳኛ ያልሆነ እንዴት ብሎ ሌላውን ሊዳኝ ይችላል? ሕሊናን የጣለ ሰው መሪ ከሌለው መርከብ ጋር ተመሳሳይ ነው፤ ከአደጋ አያመልጥም:: ሲሳሳት የማይጸጸት ሰው ሕሊናውን ጥሏልና ከሰው ተራ ወጥቷል:: መኻል ላይ የቆሙ ሰዎች ብዙዎችን ከስህተት ይታደጋሉ:: በጎ ሕሊና ያላቸውና መኻል ላይ የቆሙ ሰዎች (ወላዋይ ማለቴ አይደለም) ኖረው ቢሆን ኖሮ ብዙ ወገኖቻችን በሕይወት ይኖሩ ነበር:: 
 
በመጨረሻም፥የተጀመረው ለውጥ ግንባር ቀደም መሪዎች ከላይ የዘረርኳቸው ተቋማት ፍሬ እንዲያፈሩ የድርሻቸውን ይወጣሉ የሚል እምነት አለኝ:: ነገር ግን እንደ ቀደምቶቹ ባለጊዜዎችና ጉልበተኞች፥ መኻል ላይ የቆሙትን በማሸማቀቅ፥ የሰውም የተቋማትም ዳኞች ማፍራት እንዳንችል ቢያደርጉ፥ የታሪክ አቅጣጫን የሚዘውር፣ መንግሥታትን የሚያስነሳና የሚጥል ፈጣሪ የምን ጊዜም ዳኛ መሆኑን መርሳት የለባቸውም:: የእርሱ ዳኝነት በዚህም በወዲያኛው ዓለም ነውና በተቻለን መጠን በእርሱና በሰዎች ዘንድ በጎ ሕሊና እንዲኖረን መትጋት ለሁላችንም ይበጃል::
 
  
0 Comments

    Amharic

    Archives

    January 2022
    October 2020
    August 2020
    April 2020
    November 2019
    September 2019
    July 2019
    April 2019
    November 2018
    October 2018
    September 2018
    August 2018
    July 2018

    Categories

    All
    Current Affairs
    Sport
    The God Factor Forum

    RSS Feed

Copyright © 1999 - 2023
  • ደወል